ከአኃው አንዱ አባ ሰርማጣን ቸልተኛ ነኝ እበላለሁ እጠጣለሁ እተኛለሁ የተረጋጋ ልብ የለኝም ምን ላድርግ? ባለው ጊዜ የሰጠው ምክር ነው።
እሱም ሦስት ነጥቦችን ነግሮታል።
፩ ተዐገሥ ውስተ በአትከ – በበአትህ ጽና
“ሑር ሕዝብየ ወባእ ቤተከ ወዕፁ ኆኅተከ ወተኀባዕ ኅዳጠ ምዕረ – ወገኔ ሆይ ሂድ ወደቤትህ ግባ ደጅህን ዝጋ ጥቂት ጊዜ ተሸሸግ” እንዲል ኢሳ ፳፮፥፳፤
የዚህም ምሥጢሩ “አስተጋብእ ሕዋሳቲከ – ሕዋሳትህን ሰብስበህ” ጸልይ ማለት ነው። አንድም የጸሎቱን አንቀጽ ስልቱንና ምሥጢሩን አውቀህ ጸልይ ማለት ነው።
በቅዱስ ወንጌልም የተመዘገበው በተመሳሳይ መልኩ “ባእ ቤተከ ወዕፁ ኆኅተከ ወጸሊ ኀበ አቡከ በኅቡእ የዐሥየከ ክሡተ – ወደቤትህ ግባ ደጅህን ዝጋ ወደአባትህ በሥውር ጸልይ በግልጥ ይሰጥሃል” ተብሎ ነው ማቴ ፮፥፮
፪ ወዘክህልከ ግበር ዘእንበለ ሁከት – ያለመታወክ የተቻለህን አድርግ
፫ ወዝንቱ ግብር ኅዳጥ ዘትገብሮ ከመ ግብር ብዙኅ ዘይገብሮ እንጦንዮስ በውስተ ደብሩ – በበአትህ ጸንተህ የምትሠራው ጥቂቱ ሥራ እንጦንስ በበአቱ ሆኖ እንደሚሠራው ብዙ ሥራ ነው ማለት እንደሱ ይሆንልሃል።
እስመ ዘይፈቅድ ይግበር ዘኮነ ወኢይክል ይትዔረዮ ለዘይክል ወይገብር – የታዘዘውን ሊሠራ የሚወድ ግን አልቻለው ብሎ የሚቀርበት ሰው ተችሎት የሚሠራውን ሰው ይተካከለዋልና።
የምንችለውን ማድረግ እንዴት ይገለጣል?
፩ ለትምህርተ ወንጌል/ለጉባኤ ወንጌል የምንሰጠው ክብርና ትኩረት፤
ጽድቅኬ ኢኮነ በአምጣነ ምግባረ ሥጋ – ጽድቅ በሥራ ብዛት አይደለም።
ማርያምሰ ተልእከት በመንፈሳ ለመንፈሳውያት ዘውእቱ ሰሚዐ ቃለ እግዚእ – ማርያም በመንፈሷ መንፈሳዊነትን አገለገለች ይኸውም ቃለ እግዚአብሔር መስማት ነው።
፪ የስጦታችን ዐይነትና መጠን፤
ጽድቅኬ ኢኮነ በብዝኃ አቅርቦ – ጽድቅ ብዙ በመስጠት አይደለም
እስመ እግዚእነ በእንተ በዓልተ ክልኤ ጸሪቅ ከመ ይእቲ አብአት ፈድፋደ እምአብዕልት – ጌታችን ሁለት መሐልቅ የሰጠችውን መበለት ብዙ ከሰጡት እሷ ብዙ እንደሰጠች ተናግሯልና።
፫ ትሕትናችንን የምንገልጥበት ሁናቴ
መጽብሐዊኒ በእንተ ትሕትናሁ ጸድቀ እምፈሪሳዊ ዘበዝኀ ጾሙ ወምጽዋቱ ወጸሎቱ – ቀራጩም ስለትሕትናው ብዙ ምጽዋት፣ ጾምና ጸሎት ካለው ፈሪሳዊ ጻድቅ ሆኖ ተመልሷል።
ቴዎፍሎስ አንዱን አበ ምኔት ከሰው ተለይተህ በጽማዌ ውስጥ ሆነህ ምን አገኘህ ብሎ ቢጠይቀው፦
አነውር ርእስየ በኵሉ ጊዜ – በየጊዜው ራሴን መንቀፍን አገኘሁ ብሎታል
፬ ጥፋታችንን የምናምንበት መንገድ
ፈያታዊኒ ዘየማን ዘለፈ ርእሶ በጊዜ ሞቱ – ፈያታዊ ዘየማን በጊዜ ሞቱ ራሱን ዘልፏል (ንሕነ ተፈደይነ በከመምግባሪነ) ብሎ
ወበእንተዝ ደለዎ ገነት – ስለዚህ ገነት ተገባው።
ይቆየን



Leave a Reply