፴፰.፩ በ (፭/ር) ግነዩ ለእግዚአብሔር ወጸውዑ ስሞ ወንግርዎሙ ለአሕዛብ ምግባሮ ሀቡ ስብሐተ ለስሙ አክብሩ ሰንበተ ተገበሩ ጽድቀ ዝግቡ ለክሙ መዝገበ ዘበሰማያት ኀበ ፃፄ ኢያማስኖ ወኢይረክቦ ሰራቂ ድልዋኒክሙ ንበሩ ዘበላዕሉ ሀልዩ ኀበ ሀሎ ክርስቶስ።
ትርጉም፦
ለእግዚአብሔር ተገዙ ስሙንም ጥሩ ሥራውን ለአሕዛብ ንገሯቸው ለስሙ ምስጋናን ስጡ/አቅርቡ ሰንበትን አክብሩ ጽድቅን ሥሩ ሌባ በማያገኘው ብል በማያጠፋው በሰማያት መዝገብን አከማቹ ክርስቶስ ባለበት ለመሆን በላይ ያለውን እያሰባችሁ ተዘጋጅታችሁ ኑሩ።
፴፰.፪ የዕለቱ ምንባባት፦
፩ተሰ ፬፥፩ – ፲፫፤
፩ጴጥ ፩፥፲፫ – ፍ፤
ግብ ፲፥፲፯ – ፴፤
ወንጌል፦ ማቴ ፮፥፲፯ – ፳፭
ቅዳሴ፦ ዘኤጲፋንዮስ
፴፰.፫ የዕለቱ ምስባክ፦
እግዚአብሔርሰ ሰማያተ ገብረ፤
አሚን ወሠናይት ቅድሜሁ፤
ቅድሳት ወዕበየ ስብሐት ውስተ መቅደሱ። መዝ ፺፭፥፭
ትርጉም፦
እግዚአብሔር ግን ሰማያትን ፈጠረ፤
እምነትና በጎነት በፊቱ ናቸው፤
ቅድስና እና የክብር ገናንነት በመቅደሱ ውስጥ ናቸው።
ምሥጢር፦
እግዚአብሔር ሰባቱን ሰማያት ፈጠረ፤
ሃይማኖት ምግባር በፊቱ ነው አለ ምግባር ሃይማኖት የያዘ ሰውን ይወዳል፤
ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ ተብሎ መመስገን ዐቢየ ስብሐት መባል ገንዘቡ ነው።
፴፰.፬ መልእክት፦
ሰማይ ማለት ሥዕለ ማይ – የውኃ ንድፍ ማለት ነው አንድም ልዑል ማለት ነው። ቀለሙ/መልኩ ሰማያዊ ነው እጅግ ብሩህ ቢሆን ዐይን ይበዘብዝ ነበርና እጅግም ጨለማ ቢሆን ለዐይን ይከብድ ነበርና። ይህንንም የፈጠረው የዐይን ማረፊያ ይሆን ዘንድ ነው፤ ጠፈር/ሰማይ ባይኖር የሰው የእንስሳ የአራዊት ዐይን ሁሉ ማረፊያ አጥቶ ወልቆ ወልቆ በወደቀ ነበርና።
ይህ ለሥጋዊ እንቅስቃሴአችን ሲሆን ለመንፈሳዊው እንቅስቃሴያችን ደግሞ በተለይ በጊዜ ቅዳሴ የዐይናችን ማረፊያ የሚሆነው ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙ ነው። አምላክችን ምግባር ከሃይማኖት አንድ አድርጎ የያዘ ሰውን ይወዳል ባልነው መሠረት አስቀድሳለሁ ብሎ ከቤቱ ተዘጋጅቶ ወደ ቤተ ክርስቲያን የሚመጣ ሰው በዕለቱ የታወቀና ድንገተኛ ነገር ካላጋጠመው በስተቀር ሥጋ ወደሙን ይቀበል ዘንድ ወዶና ፈቅዶ የሚኖርበት ክርስቲያናዊው ሕግ ያስገድደዋል ይህን ካላደረገ ዐይኑ ማረፊያ ያጣ ሰው ሆኗል።
“እግዚአብሔርሰ ሰማያተ ገብረ – እግዚአብሔርማ ሰማያትን ፈጠረ” ብሎ ለመዘመር አቅም የሚያንሰው ይሆናል። ዐይናችን ማረፊያ ሲያገኝ ልባችንም በተስፋ የተመላ ይሆናል፤ እንዲህ ከሆነ ዐይን ያላያትን በሰው ልብ ያልታሰበችውን እግዚአብሔር ለወዳጆቹ ያዘጋጃትን ዘለዓለማዊት መንግሥት በተስፋ እየጠበቀ የመኖር ዕድሉ ከቀን ወደቀን ያድጋል “ትምጻእ መንግሥትከ – መንግሥትህ ትምጣልን” እያለ ይጸልያልና።


Leave a Reply