ኅሥሥ ህላዌ ርእስከ ወአስተሐይፅ በጥዩቅ ወአንተ ትኔስሕ እስመ አልቦ ዘይወስድ ኀበ ምግባረ ጽድቅ ከመ ተዘክሮ ኃጣውእ
– ስለሰው ማውራትህን ትተህ የራስህን አኗኗር መርምር ኃጢአተኛ እንደሆንህ አንድም ፈራሽ በስባሽ እንደ ሆንህ እወቅ ከዚህ ደረጃ ከደረስህ ሰውን ከመንቀፍ ራስህን ወደመንቀፍ ትመለሳለህ የራስን ኃጢአት እንደማሰብ ትሩፋት ወደመሥራት የሚያደርስ የለምና። ተግሣጽ ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ፳፫
በሕይወታችን በማይመለከተንና ምንም ትርፍ በማናገኝበት ጉዳይ እየገባን እንዲባክን ያደርግነው ጊዜ ቀላል አይደለም። የጊዜው መባከን ብቻ ሳይሆን በመንፈሳዊ ሕይወታችን ላይ ያሳደረው አሉታዊ ተጽእኖ በቀላሉ የሚታይ አይደለም። ብዙ ሰው በቤቱ ውስጥ የሚኖረው በአካሉ ነው እንጅ በልቡ ሌላ ቦታ ነው። የያዘውን የሚጥለው፣ የማያገኘውን የሚፈልገው፣ ያለበትን የሚረሳው፣ መሄድ ወደሚገባው በየምክንያቱ እየቀረ መሄድ ወደማይገባው የሚሄደው፣ በማያስጨንቀው የሚጨነቀው የራሱ በሆነው ጉዳይ አይደለም። ለሱ የተደረገለትን ከማሰብና በዚያ ከማመስገን ይልቅ ሌላ ሰው ላይ ያየው ነገር እያስቀናው ደስታውን በራሱ ያጣል። አልገባውም እንጂ ሌሎችም በእሱ እየቀኑ ደስታቸውን ያጣሉ። ለዚህ ነው ሊቁ ከእንዲህ አይነቱ ውጣ ውረድ ወጥተን የራሳችንን ኃጢአት እያሰብን የትሩፋት ሥራዎችን ወደመሥራት እንድናድግ የመከረን። ራስን መሆን ትልቅ ነገር ነው የትም ስንሄድ የምናገኘው ራሳችንን ነውና። ኅሥሥ ህላዌከ – ኑሮህን ፈልግ ማለት ይሄ ነው። እኛስ ሀገራችን በሰማይ ነው እንዳለ ሐዋርያው። እዚያ ለመግባት የሚያስችል ዝግጅት አድርጌያለሁ? ብሎ ራስን መጠየቅ ለራስ ጊዜ እንዲሰጡ ያደርጋል። በኪራይ ቤት የሚኖር ሰው ለሚቀጥለው የሚሆን ክፍያ አለኝ ብሎ ካሰበ ጊዜው ሲደርስ አይጨነቅም። በተጠየቀ ጊዜ ካስቀመጠው አንሥቶ ይሰጣልና።



Leave a Reply to ግሩምCancel reply